ጊዜያችንን ጠብቀን ወደ እናንተ ለመድረስ ያደረግነው ጥረት ተሳክቶ የመጋቢትን ወር ዕትም እነሆ በእንዲህ መልኩ ይዘን መጥተናል:: በእስከዛሬው የአንድ ዓመት ከመንፈቅ ጉዟችን ብርታታችንንም ሆነ ድክመታችንን እየነገራችሁን ጉዟችን እንደቀጠለ ነው:: እናመሰግናለን::
በመጽሔታችን የተለያዩ ምሁራን በታሪክ፣ በባህል፣ በኪነ-ጥበብ፣ በፍልስፍና፣ በቅርስ እና በሌሎች ማህበራዊ ጉዳዮች የሚያነሱት ሀሳብ መማማርን ፈጥሯል:: የነገሮችን ሚዛናዊነት በመጠበቅ እውነታን ማሳየት፣ ፍቅርን፣ ሠላምን፣ አንድነትን በአጠቃላይ ኢትዮጵያውነትን ማንገስ ነው አላማችን::
የዚህ መጽሔት ቋሚ አምደኞቻችን የየራሳቸው የፈቃድ ኃላፊነት አለባቸው:: ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ በዚህ ዕትም ኢትዮጵያውነትን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንዴት እንደተጠበቀ ያሳዩናል:: ለአርባ ዓመታት ማንነታቸውን ሳይገልፁ የኖሩት አሸናፊ ዘደቡብ አ.አ ከነ ፎቷቸው በመጽሔታችን ብቅ ብለዋል:: ቋሚ አምደኝነታቸው ይቀጥላል::
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የተፈጥሮ ሳይንስ ሙሁር እና ተመራማሪ ፕሮፌሰር ሽብሩ ተድላ በጥልቅ ፍተሻ ጥናት ላይ ተመስርተው ተውሳክ እና ታሪክ በቁንጽል የሚሉት አላቸው::
እንደሌሎቹ ቋሚ አምደኞቻችን ሁሉ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሥነ-ጽሑፍ መምህሩ ዶክተር መሀመድ ዓሊ አንዲት የጥበብ ስራ አድርሰውናል:: የመቐለ ዩኒቨርስቲ የፍልስፍና መምህሩ እያሱ ባሬንቶ የኢትዮጵያ ፍልስፍና በሐተታ ዘርዓ ያዕቆብ ፈትለ ነገር ትንታኔ ውስጥ ያሳዩናል::
የስፖርት ዘጋቢው ገነነ መኩሪያ(ሊብሮ) እንዲሁም ጋዜጠኞቹ ጥበቡ በለጠ እና ሰለሞን በቀለም የየራሳቸውን ጽሑፍ ይዘው ቀርበዋል:: በአምደኝነታቸውም ይቀጥላሉ::
እንዲህ እያልን እንጓዛለን:: የጸሐፍቶችን ሀሳብ እናከብራለን:: ሌሎች ጸሐፍቶችም ወዳጅ ይሆኑን ዘንድ ጥሪ እናደርጋለን:: አስተያየታችሁ ያተጋናል፣ ሀሳባችሁ ያበረታታናል:: አሁንም አብረን እንዝለቅ::
